ህዳር 19 ቀን 2016 ዓ.ም (ኢስታንቡል)
በቱርኪዬ የኢፌዲሪ ልዩ መልዕክተኛ እና ባለሙሉ ስልጣን አምባሳደር ክቡር አደም መሐመድ የቱርኪዬ የጉዞ ወኪሎች ማህበር (TURSAB) ምክትል ፕሬዝዳንት ዳቩ ጉናይይ፣ እንዲሁም ሌሎች ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች በተገኙበት በቱሪዝም ዘርፍ አብሮ ለመስራት በሚቻልባቸዉ ጉዳዩች ዙሪያ ምክክር ተደርጓል።
በውይይቱም ክቡር አምባሳደር ቱሪዝም የአገራችን የትኩረት መስክ መሆኑን በመጠቆም እና መንግስት በዘርፉ እያከናወናቸው ስላሉ ተግባራት እንዲሁም በአገራችን ስላሉ የቱሪስት መስህቦች ሁኔታ ገለጻ በማድረግ፣ ማህበራቸው ውስጥ ያሉ የቱር ኦፕሬተሮች ኢትዮጵያን በቱር ፓኬጃቸው እንዲያስገቡ፣ በአገራችን ካሉ ቱር ኦፕሬተሮች ጋር በጋራ እንዲሰሩ የልምድ ልዉዉጥና ስልጠና ማግኘት የሚቻልበትን ሁኔታ እንዲሁም የቱር ኦፕሬተሮች ጉብኝት (familiarization trip) እንዲያደርጉ ጠይቀዋል።
የማህበሩ ምክትል ፕሬዝዳንት በበኩላቸው ለተደረገላቸው ገለፃ አመስግነው ያገኙትን መረጃ ለማህበር አባላቱ እንደሚያሰራጩ፣ ከኢትዮጵያ የቱር ኦፕሬተሮች ጋር በትብብር ለመስራት ፈቃደኛ መሆናቸውን እና በቱሪዝም መድረሻ ላይ የሚካሄድ ዉይይት በፅ/ቤታቸዉ አዳራሽ በማዘጋጀት ለማህበሩ አባላት የኢትዩጵያ የቱሪዝም መዳረሻነትን ማስገንዘብ ይቻላል ብለዋል። ለዚህም ሚስዩኑ በመረጠዉ ግዜ ፕሮግራሙን በጋራ እንደሚያዘጋጅ ቃል ገብተዋል።