ጥቅምት 08 ቀን 2016 ዓ.ም (አንካራ)
በኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ም/ቤት ፕሬዝደንት የተከበሩ ሼህ ሐጂ ኢብራሒም ቱፋ የሚመራው እና የጠቅላይ ምክር ቤቱ ዋና ፀሐፊ ሸይኽ ሐሚድ ሙሳ፣ የፕሬዚደንቱ ልዩ አማካሪ ኡስታዝ አቡበክር አህመድና ዶ/ር አብደላ ኸድርን ያካተተው የልዑካን ቡድን ለይፋዊ የስራ ጉብኝት ጥቅምት 06 ቀን 2016 ዓ.ም አንካራ፣ ቱርኪዬ የገባ ሲሆን፣ በአንካራ የኢፌዲሪ ባለሙሉስልጣን አምባሳደር ክቡር አደም መሐመድ እና የሚስዮኑ ዲፕሎማቶች አቀባበል አድርገውላቸዋል።
በአንካራ የኢፌዲሪ ባለሙሉ ስልጣን አምባሳደር ክቡር አደም መሐመድ ለልዑካን ቡድኑ አባላት በቱርክዮና ኢትዮጵያ መሀከል ስላለው ግንኙነት፣ ለትምህር በሚመጡ ተማሪዎች ጉዳይ እንዲሁም በቱርክዮ ሊገኝ ስለሚችሉ ጥቅሞች ዙሪያ በፅ/ቤታቸው ገለፃ አድርገውሏቸዋል።
በኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ም/ቤት ፕሬዝደንት የተከበሩ ሼህ ሐጂ ኢብራሒም ቱፋ በበኩላቸው ለተደረገላቸው ደማቅ አቀባበል እና ለተደረገላቸው ገለፃ አመስግነው የሁለትዮሹን ግንኙነት በማጠናከርና በተማሪዎች ዙሪያ በተነሳው ጉዳይ ከሚመለከታቸው አካለት ጋር እንደሚመክሩበት ገልፀዋል።
የልዑካን ቡድኑ በቱርኪዬ በነበረውን የ 3 ቀን ቆይታ ከቱርኪዬ የሃይማኖት ጉዳዮች ፕሬዝደንት ፕሮፌሰር ኢርባሽ፣ ከቱርኪዬ ዲያኔት ፋውንዴሽን ዋና ስራ አስኪያጅ ኢዛኒ ቱራን፣ እንዲሁም ከኮንያ ከተማ ኢፍታእ ማዕከል ኃላፊ ሙፍቲ ፕሮፌሰር ዶ/ር ዓሊ ኦክ ጋር በተለያዩ ጉዳዮች ዙሪያ ፍሬያማ ውይይት አድርገዋል።
ከውይይቱ ጎን ለጎን በአገሪቱ ቤተ መንግሥት ውስጥ የሚገኘዉን ግዙፍ መስጂድ፣ የቁርኣን ተህፊዝ መድረሳና ግዙፉን የሀገሪቱ ቤተ መጻሕፍት፣ እንዲሁም በታሪካዊቷ ኮንያ ከተማ የሚገኙ የተለያዩ እስላማዊ ማዕከላትን እና ተቋማትን ጎብኝተዋል።